Wednesday, December 26, 2012


From:ethiopianreporter.com 



የብሔራዊ ቡድን ተጫዋቾችና አሠልጣኞች ከ2.7 ሚሊዮን ብር በላይ ሽልማት ተሰጣቸው

በ16/04/2005  ማምሻውን በኢንተርኮንትኔንታል ሆቴል በተካሄደው ሥነ ሥርዓት የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ለብሔራዊ ቡድን ተጫዋቾች አሠልጣኞች፣ የቡድን መሪዎችና ድጋፍ ሰጪዎች ከ2.7 ሚሊዮን ብር በላይ ሽልማት ሰጠ፡፡
በተለያዩ እርከኖች በተከፋፈለው ሽልማት መሠረት የብሔራዊ ቡድኑ ዋና አሠልጣኝ ሰውነት ቢሻው 280 ሺሕ ብር የሚያወጣ ሊፋን መኪና ሲሸለሙ፣ ለቡድኑ ሦስት ግቦችን ያስቆጠረው አዳነ ግርማ 130 ሺሕ ብር አግኝቷል፡፡ ከእሱ በመቀጠል ጌታነህ ከበደና ሥዩም ተስፋዬ 110 ሺሕ ብር በነፍስ ወከፍ ሲያገኙ ሳላዲን ሰይድ 90 ሺሕ ብር ተሸልሟል፡፡ ሽልማቱ የተሰጠው በተጫወቱበት ሰዓትና ባስቆጠሩት ግብ ብዛት መሆኑም ተገልጿል፡፡ በዚህ መሠረት አዳነ 100 ሺሕ ብር ሲደመር ለሦስት ግቦች 30 ሺሕ ብር፣ ሳላዲን 80 ሺሕ ብር ሲደመር ለአንድ ግብ አሥር ሺሕ ብር መሸለሙን ማወቅ ተችሏል፡፡ ለአንድ ግብ 10 ሺሕ ብር ሽልማት ተሰጥቷል፡፡

አምስት ተጫዋቾች እያንዳንዳቸው 50 ሺሕ ብር ሲያገኙ፣ አራት ተጫዋቾች እያንዳንዳቸው 80 ሺሕ ብር አግኝተዋል፡፡ ስድስት ተጫዋቾች በነፍስ ወከፍ 90 ሺሕ ብር ሲያገኙ፣ 11 ተጫዋቾች እንዲሁ ከ100 ሺሕ እስከ 130 ሺሕ ብር ተሸልመዋል፡፡ የቡድኑ ምክትል አሠልጣኝ ሥዩም ከበደ 150 ሺሕ ብር ሲሸለሙ፣ በተለያዩ ጊዜያት የቡድን መሪ የነበሩ ሁለት ግለሰቦች እያንዳንዳቸው 25 ሺሕ ብር ተሸልመዋል፡፡

የብሔራዊ ቡድኑ ሐኪም ዶክተር ተረፈ ጣፋ 50 ሺሕ ብር ሲሰጣቸው፣ ወጌሻው ይስሀቅ ሽፈራው 100 ሺሕ ብር ተሸልመዋል፡፡ የሥነ ልቦና ባለሙያው 15 ሺሕ ብር፣ የሥነ ምግብ ባለሙያው 15 ሺሕ ብር፣ የትጥቅ ኃላፊው 10 ሺሕ ብር ሽልማት አግኝተዋል፡፡

በሽልማት ሥነ ሥርዓቱ ላይ ለብሔራዊ ቡድኑ አባላት ሽልማት የሰጡት የፌዴሬሽኑ ፕሬዚዳንት አቶ ሳህሉ ገብረወልድ ባደረጉት ንግግር ጥር 4 ቀን 2005 ዓ.ም. በሚሊኒየም አዳራሽ ለብሔራዊ ቡድኑ አሸኛኘት ይደረጋል ብለዋል፡፡ “ጥር 4 ቀን በሚሊኒየም አዳራሽ ለብሔራዊ ቡድኑ አሸኛኘት በሚደረገው የእራት ግብዣ ላይ ሼክ መሐመድ አል አሙዲ ለቡድኑ አባላት አምስት ሚሊዮን ብር ይሰጣሉ፤” ሲሉም ተናግረዋል፡፡

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በደቡብ አፍሪካው የአፍሪካ ዋንጫ ናይጄሪያ፣ ዛምቢያና ቡርኪና ፋሶ የሚገኙበት ቡድን ውስጥ ተደልድሏል፡፡ እስካሁን ድረስ የወዳጅነት ጨዋታ ሳያደርግ በልምምድ ላይ የሚገኘው ብሔራዊ ቡድኑ ከኒጀር፣ ከቶጎና ከቱኒዝያ ጋር እዚህ አዲስ አበባ የወዳጅነት ጨዋታ ያደርጋል ተብሎ እየተጠበቀ ነው፡፡

ባለፈው ሳምንት የብሔራዊ ቡድኑ ተጫዋቾች ቃል የተገባላቸው ሽልማት ባለመሰጠቱ ለአንድ ቀን አድማ ማድረጋቸው ይታወሳል፡፡ ፌዴሬሽኑ ይኼንን ቁጣ ለማብረድ ሲል የትናንቱን ሽልማት መስጠቱ ተሰምቷል፡፡ ተጫዋቾቹ ቢታገሱ ኖሮ ከዚህ የተሻለ ሽልማት ያገኙ እንደነበር የፌዴሬሽኑ ኃላፊዎች ተናግረዋል፡፡ ፌዴሬሽኑ ተጫዋቾቹ ውጤት ካመጡ ከፍተኛ ሽልማት እንደሚጠብቃቸው እየተናገረ ነው፡፡ ይኼ ሽልማት ተጫዋቾቹ ሕዝቡ በጉጉት የሚጠብቀውን ውጤት እንዲያገኙ እንደማንቂያ ተቆጥሯል፡፡ በፌዴሬሽኑና በተጫዋቾቹ መካከል እንደ ቃል ማሰሪያ መሆኑም በሥነ ሥርዓቱ ላይ ተገልጿል፡፡

ሪፖርተር ያነጋገራቸው ተጫዋቾች በተሰጣቸው ሽልማት ደስተኛ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ በአፍሪካ ዋንጫ ውድድር ተሳትፏቸው በተቻላቸው መጠን አገሪቷን የሚያኮራ ውጤት ለማስመዝገብ ብቁ ተፎካካሪ ሆነው እንደሚቀርቡም ተናግረዋል፡፡ 

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በደቡብ አፍሪካ በሚካሄደው የአፍሪካ ዋንጫ ውድድር እንዲረዳው በአሁኑ ጊዜ የተለያዩ ዓይነት ሽልማቶች የሚያስገኙ ዕጣዎች ተዘጋጅተው ሕዝቡ በስልክ መልዕክት እያስተላለፈ ገቢ እየተሰበሰበ ሲሆን፣ በደሌ ቢራም ለሁለት ዓመታት ስፖንሰር በመሆን 24 ሚሊዮን ብር ድጋፍ የሚያስገኝ የፊርማ ሥነ ሥርዓት የተደረገው በቅርቡ ነው፡፡  

No comments:

Post a Comment