Monday, December 31, 2012


from: ethiopianreporter.com

የንብ ባንክ ፕሬዚዳንት ኃላፊነታቸውን ለቀቁ

•    አዲሱ ተጠባባቂ ፕሬዚዳንት ነገ ርክክብ ይፈጽማሉ
በአገሪቱ ከሚገኙ የግል ባንኮች መካከል በቀዳሚነት የሚጠቀሰው ንብ ኢንተርናሽናል ባንክን ከማደራጀት ጀምሮ እስከ ፕሬዚዳንትነት ሲመሩት የቆዩት ታዋቂው የባንክ ባለሙያ አቶ አመርጋ ካሳ ኃላፊነታቸውን ለቀቁ፡፡

“ቀድሞም ቢሆን ሽግግርና መተካካት እንዲኖር የቦርዱም የእኔም ፍላጎት ነበር”አቶ አመርጋ ካሳን ተክተው ከነገ ጀምሮ የንብ ባንክ ተጠባባቂ ፕሬዚዳንት ሆነው እንዲሠሩ የባንኩ ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ ክብሩ ፎንጃ ተሰይመዋል፡፡ ባለፈው ሐሙስ አቶ አመርጋና አቶ ክብሩ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ እንደተገለጸው፣ አቶ አመርጋ ኃላፊነታቸውን በይፋ በነገው ዕለት ያስረክባሉ፡፡

አቶ አመርጋ ንብ ባንክን ለማቋቋም በመሥራችነትና በአደራጅነት ከዚያም በምክትል ፕሬዚዳንትነትና ላለፉት ሰባት ዓመታት ደግሞ በፕሬዚዳንትነት በአጠቃላይ ለ15 ዓመታት ማገልገላቸውን፣ ባንኩን የለቀቁትም በገዛ ፈቃዳቸው መሆኑንም ገልጸዋል፡፡

የሥልጣን ሽግግሩ ሰላማዊ በሆነ መንገድ የሚከናወንና የመተካካት ባህልን ለማዳበር ጭምር የተወሰደ ዕርምጃ ነው ተብሏል፡፡ እንደ አቶ አመርጋ ገለጻ፣ በመስከረም 2005 ዓ.ም. ለባንኩ ቦርድ በጻፉት ደብዳቤ ኃላፊነታቸውን ለማስተላለፍ የፈለጉት ቀሪ ዘመናቸውን ከቤተሰባቸው ጋር ማሳለፍ በመፈለጋቸው መሆኑን ይጠቁማል፡፡

“ከቤተሰብ ጋር ጊዜዬን ለማሳለፍ በመፈለጌ ራሴ ባቀረብኩት ጥያቄ መሠረት የባንኩ ዳይሬክተሮች ቦርድ ነገሩን ካጤነና የጡረታ መውጫ ጊዜዬን አገናዝቦ ለጥያቄዬ አዎንታዊ መልስ ሰጥቷል፤” ብለዋል፡፡ በመስከረም 2005 ዓ.ም. መጀመሪያ አካባቢ ለቀረበው ጥያቄም ቦርዱ አዎንታዊ ምላሹን የሰጠው በጥቅምት 2005 ዓ.ም. መጀመሪያ ላይ ነው፡፡

በአብዛኛው በአገሪቱ ውስጥ ያሉ የባንክ መሪዎች ከኃላፊነታቸው የሚነሱት በተፅዕኖና በተለያዩ ግፊቶች ስለሆነ፣ የአቶ አመርጋ ካሳ ከኃላፊነት መልቀቅ ከቤተሰብ ጉዳይ ጋር በተያያዘ  ብቻ ነው ወይ? የሚል ጥያቄ ቢያስነሳም፣ አቶ አመርጋ ግን የእርሳቸው ከኃላፊነት መልቀቅ ሌላ ምንም ምክንያት የሌለው እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ ከባንኩ ቦርድ የተገኘውም መረጃ ይህንኑ የአቶ አመርጋን ሐሳብ የሚያጠናክር ነው፡፡ በኢንዱስትሪው ውስጥ ያሉ ባለሙያዎች አቶ አመርጋ ሳይገፉ መውጣታቸው መልካም ዕድል ነው ብለዋል፡፡

የአቶ አመርጋ ከኃላፊነት መልቀቅ ጉዳይ ውሳኔ ከተሰጠው ወደ ሁለት ወራት አካባቢ የሆነው ሲሆን፣ ጉዳዩ ይመለከታቸዋል የተባሉና ከባንኩ ጋር ግንኙነት ያላቸው ተቋማት እንዲያውቁት የተደረገው ደግሞ ኅዳር 10 ቀን 2005 ዓ.ም. ነው፡፡

በባንኩ የቦርድ ሊቀ መንበር በአቶ ታደሰ ቦጋለ የተጻፈው ደብዳቤ፣ በአገሪቱ ውስጥ ያሉ ሁሉም ባንኮች አቶ አመርጋ ከታኅሳስ 22 ቀን 2005 ዓ.ም. ጀምሮ ኃላፊነታቸውን መልቀቃቸውንና ለአዲሱ ተጠባባቂ ፕሬዚዳንት አቶ ክብሩ የሚያስረክቡ መሆኑን አስታውቋል፡፡

በኢትዮጵያ የባንክ ኢንዱስትሪ ውስጥ በተለያዩ የሥራ ኃላፊነት ከ40 ዓመታት በላይ አገልግሎት ያላቸው አቶ አመርጋ በብሔራዊ ባንክ ከ25 ዓመታት በላይ ሠርተዋል፡፡ በብሔራዊ ባንክ አገልግሎት ዘመናቸው የውጭ ምንዛሪ መምርያ ኃላፊ ሆነው ያገለገሉ ሲሆን፣ ከብሔራዊ ባንክ ከወጡም በኋላ ከ1983 ዓ.ም. ጀምሮ በኢትዮጵያ የመጀመሪያው የግል ባንክ በመሆን የተቋቋመው የአዋሽ ባንክ መሥራች አባል ናቸው፡፡ ከዚህም በኋላ ንብ ባንክን ወደ ማደራጀት እስከገቡበት ጊዜ ድረስ የአዋሽ ባንክ ምክትል ሥራ አስኪያጅና የቦርድ አባል በመሆንም አገልግለዋል፡፡

ከአዲሱ የንብ ባንክ ተጠባባቂ ፕሬዚዳንት ጋር በመሆን ለሚቀጥሉት ሦስት ወራት በንብ ባንክ ውስጥ የሚቆዩት አቶ አመርጋ፣ ቀጣይ የሥራ ጊዜያቸውን በተመለከተ ምንም ያሰቡት ነገር እንደሌለ ገልጸው፣ ሆኖም በማንኛውም ጊዜ የንብ ባንክ ቦርድና አስተዳደር ለማገዝ ዝግጁ መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡  

ባንኩን በተጠባባቂነት እንዲመሩ የተሰየሙት አቶ ክብሩ፣ አሁን የተመደቡበትን ኃላፊነት እንዲይዙ በአቶ አመርጋ መጠቆማቸውም ታውቋል፡፡ አቶ አመርጋም ይህንኑ አረጋግጠዋል፡፡ አቶ ክብሩ የአቶ አመርጋን ቦታ ከመያዛቸው በፊት በንብ ኢንተርናሽናል ባንክ የፋይናንስና አስተዳደር ምክትል ፕሬዚዳንት በመሆን ላለፉት ሦስት ዓመታት ሲያገለግሉ ቆይተዋል፡፡

በአገሪቱ የፋይናንስ ኢንዱስትሪ ውስጥ የሚንቀሳቀሱ ባንኮችን ለሚመሩ ባለሙያዎች የኢትዮጵያ የብሔራዊ ባንክ መመርያ የራሱ የሆነ አስተዋጽኦ አለው፡፡ አንድ የባንክ ባለሙያ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ወይም ፕሬዚዳንት ለመሆን የ16 ዓመታት ልምድ የሚያስፈልገው መሆኑን የብሔራዊ ባንክ መመርያ ይደነግጋል፡፡ ይህ ድንጋጌ ግን በኢንዱስትሪው ውስጥ ወጣቶች ወይም ተተኪዎች እንዳይኖሩ አድርጓል የሚል አስተያየት በተደጋጋሚ ቢሰጥም፣ አቶ አመርጋ ባንካቸው ተተኪዎችን ከሥር የማፍራት ሥራ ሲሠራ መቆየቱን ተናግረዋል፡፡ መመርያው ወጣቶችን የሚያበረታታ አይደለም የሚል ትችት ቢሰነዘርበትም፣ ዘርፉ ጥንቃቄ የሚጠይቅ በመሆኑ የብሔራዊ ባንክ ዕርምጃ ትክክል ነው የሚሉ አሉ፡፡

የአቶ አመርጋን ከኃላፊነት መልቀቅ በተመለከተ አስተያየት የሰጡ የባንክ ባለሙያዎች እንደገለጹት፣ አቶ አመርጋ በሰላማዊ መንገድ ኃላፊነታቸውን ማስረከብ መቻላቸው እንደ ልዩ ዕድል የሚቆጠር ነው፡፡ ለዚህም የሰጡት ምክንያት በኢትዮጵያ የፋይናንስ ኢንዱስትሪ ውስጥ በተለይ የባንኮች መሪዎች በተለያዩ ተፅዕኖዎች ኃላፊነታቸውን የሚለቁ በመሆኑ ነው፡፡ በሌላ በኩል ብዙ የባንክ መሪዎች ባሉበት የኃላፊነት ቦታ እስኪወገዱ ድረስ የመጠበቅ ልምድ ያለ ሲሆን፣ እንደ አቶ አመርጋ ኃላፊነትን በሰላማዊ መንገድ የማስረከብ ልምድ መዳበር እንዳለበት፣ በዕድሜ የገፉ ባለሙያዎችም ለተተኪዎች ኃላፊነታቸውን ማስረከብ ይኖርባቸዋል ብለዋል፡፡

የአቶ አመርጋን ከኃላፊነት መልቀቅ ተከትሎ አዲሱ የንብ ባንክ ተጠባባቂ ፕሬዚዳንት፣ ንብ ኢንተርናሽናል ባንክ በአገሪቱ ውስጥ አንጋፋ ከሚባሉ የግል ባንኮች ምድብ ውስጥ ያለ ነው ብለው፣ ከባንኩ ምሥረታ ጀምሮ አቶ አመርጋ ዕውቀታቸውንና ጊዜያቸውን ሳይቆጥቡ ጉልህ አስተዋጽኦ ማድረጋቸውን አስረድተዋል፡፡ አቶ አመርጋ ከሌሎች የሥራ አጋሮቻቸው ጋር በመሆን ባደረጉት ጥረት ባንኩ አሁን ያለበት ደረጃ እንዳደረሱትም ይገልጻሉ፡፡ በቀጣይም ከአቶ አመርጋ የተረከቡትን ኃላፊነት በብቃት ለመወጣት ጥረት እንደሚያደርጉ አመልክተዋል፡፡ አያይዘውም አቶ አመርጋ እዚህ ያደረሱትን ባንክ በዕረፍት በሚቆዩበት ጊዜ ጭምር እየተከታተሉ ድጋፍ ያደርጋሉ የሚል ዕምነት ያላቸው መሆኑን የገለጹት ተጠባባቂ ፕሬዚዳንቱ፣ የዕረፍት ጊዜያቸው መልካም እንዲሆን ተመኝተውላቸዋል፡፡

ተጠባባቂ ፕሬዚዳንቱ አዲሱን ሥራ ከተሰናባቹ ፕሬዚዳንት አቶ አመርጋ ጎን በመሆን ለሁለት ወራት ያህል ሲለማመዱ መቆየታቸውንና ሙሉ የሥልጣን ርክክቡ የሚከናወነውም ነገ ታኅሳስ 22 ቀን 2005 ዓ.ም. መሆኑ ተገልጿል፡፡ አዲሱ ተጠባባቂ ፕሬዚዳንት አቶ ክብሩ በኢኮኖሚክስ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ያገኙ ሲሆን፣ ሁለተኛ ዲግሪያቸውን በኢኮኖሚክስና ፖሊሲ ማኔጅመንት ከጋና ዩኒቨርሲቲ አግኝተዋል፡፡ በኢትዮጵያ ልማት ባንክ በተለያዩ የኃላፊነት ቦታዎች ለ25 ዓመታት አገልግለዋል፡፡ በንብ ባንክ ውስጥ ደግሞ በምክትል ፕሬዚዳንትነት ሦስተኛ ዓመታቸውን ይዘዋል፡፡ 

No comments:

Post a Comment