Sunday, December 16, 2012

ከውጪ ንግድ ከ955 ሚሊየን ዶላር በላይ ገቢ ተገኘ

አዲስ አበባ- በዘንድሮው በጀት ዓመት የመጀመሪያ አራት ወራት ወደ ውጪ ከተላኩ የተለያዩ ምርቶች 955 ነጥብ 5 ሚሊየን የአሜሪካን ዶላር ገቢ መገኘቱን የንግድ ሚኒስቴር አስታወቀ።
የሚኒስቴሩ ምክትል የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ አብዱራህማን ሰይድ ለዋልታ ኢንፎርሜሽን ማዕከል እንደገለፁት፤ ገቢው የተገኘው ቡና፣ ወርቅ፣ ጫት፣ የቅባት እህሎች፣ የጥራጥሬ ሰብሎች፣ የቁም እንስሳት፣ የአበባና ሌሎች ምርቶችን ወደ ተለያዩ የዓለም ሀገራት በመላክ ነው።
እንዲሁም ቆዳና የቆዳ ውጤቶች፣ ጨርቃ ጨርቅና አልባሳት፣ አትክልትና ፍራፍሬ፣ ቅመማ ቅመም፣ ጥጥ፣ የተፈጥሮ ሙጫ፣ ዕጣንና ሌሎች ምርቶችም ወደ ውጪ ከተላኩ ምርቶች መካከል እንደሚገኙ አስረድተዋል።
የተገኘው ገቢ ከባለፈው አመተ ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር የዘንድሮው በ2 ሚሊየን ነጥብ 7 ዶላር ብልጫ እንዳለው ኃላፊው ተናግረው፤ ለገቢው ማደግ እንደ ቡና፣ ጥጥ፣ ጫትና ጥራጥሬ ባሉ ሰብሎች ላይ የታየው የዋጋ ጭማሪ መሆኑን ገልፀዋል።
በዕቅድ ደረጃ በአራት ወራት ውስጥ ወደ ውጭ ከተላኩ ምርቶች ለማግኘት ታስቦ የነበረው 1 ቢሊየን 420 ሚሊየን ዶላር እንደነበር ጠቁመው፤ ገዢዎች በገቡት ኮንትራት መሰረት ውል አለመፈጸም፣ በአንዳንድ ምርቶች ላይ የታየው የዋጋ መዋዥቅና በወደብ አካባቢ ተፈጥሮ በነበረ መጨናነቅ ለገቢው ማነስ ምክንያቶች ናቸው በማለት ኃላፊው መናገራቸውን ዋልታ ኢንፎርሜሽን ማዕከል ዘግቧል።

No comments:

Post a Comment