Thursday, December 27, 2012

ኢትዮጵያ 105 ሚሊዮን ብር ከጃፓን መንግሥት ድጋፍ አገኘች 
በኢትዮጵያና በጃፓን መንግሥታት መካከል የ105 ነጥብ 35 ሚሊዮን ብር የዕርዳታ ስምምነት ዛሬ በገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር ተፈረመ። የዕርዳታ ስምምነቱን የፈረሙት የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ አህመድ ሺዴና በኢትዮጵያ የጃፓን አምባሳደር ሂሮዩኪ ኪሺኖ ናቸው። በሥነ ሥርዓቱ ላይ የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ አህመድ ሺዴ እንደገለጹት በሁለቱ አገራት መካከል የተደረገው የዕርዳታ ስምምነት ጃፓን የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ለሚደረገው ጥረት ያላትን ቁርጠኝነት የሚያሳይ ነው። ከጃፓን መንግሥት የተገኘው የገንዘብ ዕርዳታ የድሀ አርሶ አደሮችን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ ለማዳበሪያ ግዢ እንደሚውልና አርሶ አደሮቹም በግብርና ምርታማነታቸው ላይ ለውጥ የሚያስገኝ መሆኑንም ገልጸዋል። ይህ የዕርዳታ ስምምነት ጃፓን ያላትን ዓለም አቀፍ ቁርጠኝነት ለማሳካትና የኢትዮጵያን የልማት ጥረቶች ለመደገፍ የምታደርገውን እንቅስቃሴ የሚያሳይ ነው ብለዋል። አቶ አህመድ እንዳሉት የጃፓን መንግሥት ለኢትዮጵያ የሚያደርገው ይፋ የልማት ድጋፍን በማጠናከር አጠቃላይ ዕርዳታ፣ ፕሮጀክት ያልሆነ ዕርዳታ፣ የምግብ ዕርዳታ፣ የምግብ ምርትን የማሳደግ ዕርዳታ በመስጠት ላይ የሚገኝ ሲሆን በፕሮጀክት ደግሞ የቴክኒክ ድጋፍ፣ የልማት ጥናትና የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ተጠቃሾች ናቸው። በኢትዮጵያ የጃፓን አምባሳደር ሂሮዩኪ ኪሺኖ በበኩላቸው የስምምነቱ ዓላማ የግብርና ግብአቶችን በማቅረብ በኢትዮጵያ የምግብ ምርትን ለማሳደግ እንደሆነም ገልጸዋል። የአነስተኛ አርሶ አደሮችን የምብርና ምርታማነትን ለማሳደግ ለኢትዮጵያ የሚደረገው የዕርዳታና የቴክኒክ ትብብር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል። ጃፓን ለበርካታ ዓመታት በኢኮኖሚና በማህበራዊ ልማት በኢትዮጵያ ውስጥ በመንቀሳቀስ ላይ እንደምትገኝም አምባሳደር ሂሮዩኪ ኪሺኖ ገልጸዋል። በኢትዮጵያ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በሚከናወነው ተግባር የማዳበሪያ ግዢው የሚፈጸመው በኢትዮጵያ የግብርና ግብአት አቅርቦት ኢንተርፕራይዝ በኩል ሲሆን የጃፓን ዓለም አቀፍ ትብብር የማዳበሪያ አቅርቦት ሂደቱን በማመቻቸት የሚሰራ ይሆናል።

No comments:

Post a Comment