Monday, December 31, 2012


from: ethiopianreporter.com

ፀረ ሙስና ኮሚሽን ትላልቅ ፕሮጀክቶችን ለመመርመር ከብሔራዊ ደኅንነት ጋር የተጣመረ ግብረ ኃይል እያቋቋመ ነው

የሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ትላልቅ የመንግሥት ፕሮጀክቶችን ለመመርመር የያዘውን ዕቅድ ለማሳካት፣ ከብሔራዊ ደኅንነት ኤጀንሲ ጋር በመቀናጀት ሥራውን የሚያካሂድ ግብረ ኃይል እያደራጀ መሆኑን ምንጮች ገለጹ፡፡ መንግሥት ከፍተኛ ገንዘብ በመመደብ ከፍተኛ የኤሌክትሪክ ኃይል፣ የስኳር ፕሮጀክቶች፣ የባቡር መስመሮችና የተለያዩ የመሠረተ ልማት ግንባታዎች እያካሄደ መሆኑ ይታወቃል፡፡ 

እነዚህ ግዙፍ ፕሮጀክቶች ከፍተኛ ገንዘብ የሚወጣባቸው በመሆናቸው የፀረ ሙስና ኮሚሽንን ትኩረት ስበዋል፡፡ ነገር ግን ኮሚሽኑ እንደተለመደው በራሱ መዋቅርና የሰው ኃይል ብቻ በእነዚህ ታላላቅ ፕሮጀክቶች ላይ ምርመራዎችን እንዲያካሂድ አልተፈለገም፡፡ ይልቁንም ምርመራው ከብሔራዊ ደኅንነት ኤጀንሲ ጋር ተባብሮ እንዲሠራ ተወስኗል፡፡ ምንጮች እንደገለጹት፣ የብሔራዊ ደኅንነት ኤጀንሲና የፀረ ሙስና ኮሚሽን ኤክስፐርቶች ተቀናጅተው እየተደራጁ መሆኑ ታውቋል፡፡

ኢትዮጵያ በ2003 ዓ.ም. የአምስት ዓመት የዕድገትና የትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ነድፋለች፡፡ በዚህ ዕቅድ መሠረት የአገሪቱን የኤሌክትሪክ ኃይል የማመንጨት አቅም ከ2,000 ሜጋ ዋት ወደ 10,000 ሜጋ ዋት ለማሳደግ ታቅዷል፡፡ የባቡር መስመርን በተመለከተ ከ2,000 ኪሎ ሜትር በላይ ለመገንባት ታቅዷል፡፡ 

እነዚህ ፕሮጀክቶች በአጠቃላይ የአገሪቱ ከፍተኛ ገንዘብ የሚወጣባቸው መሆኑ ይታወቃል፡፡ ፕሮጀክቶቹን ለማካሄድ ከፍተኛ ግዥዎች የሚካሄዱ በመሆቸው ኮሚሽኑ ምርመራ ማካሄድ እንደሚያስፈልግ በዕቅድ ይዟል፡፡ 

በእስካሁኑ ሒደት እነዚህ ዘርፎች ምርመራ ሳይካሄድባቸው የቆዩ በመሆናቸው ፀረ ሙስና ኮሚሽን ዕቅድ ይዞ በእነዚህ ዘርፎች ላይ ማተኮሩ መልካም እንደሆነ ሪፖርተር ያነጋገራቸው አስተያየት ሰጪዎች ያስረዳሉ፡፡ 

የመሠረተ ልማት ግንባታ ዘርፎች ከፍተኛ ገንዘብ የሚንቀሳቀስባቸውና ረቂቅ የሙስና ተግባራት ሊካሄዱ ስለሚችሉ፣ እንዲሁም ከፍተኛ ተሰሚነት ያላቸው ባለሥልጣናት የሚገኙበት በመሆኑ፣ የብሔራዊ ደኅንነት ኤጀንሲ በጉዳዩ እንዲገባበት ማስፈለጉን ምንጮች ጨምረው ገልጸዋል፡፡

No comments:

Post a Comment