Friday, June 14, 2013

በሙስና ወንጀል የተጠረጠሩ ግለሰቦች 92 ተሽከርካሪዎች እገዳ ተጥሎባቸዋል

በሙስና ወንጀል የተጠረጠሩ ግለሰቦች 92 ተሽከርካሪዎች እገዳ ተጥሎባቸዋል
በእነ አቶ መላኩ ፈንታ  መዝገብ ተፈፀመ በተባለው የሙስና ወንጀል በ544 ተጠርጣሪዎች ድርጅቶችና በቤተሰቦቻቸው ስም በመንግስትና በግል ባንኮች የተቀመጡ ጥሬ ገንዘብ፣ አክሲዮኖች እንዲሁም የከበሩ ማእድናት ታገዱ፡፡
በሌላ በኩል በሙስና ወንጀል ተጠርጥረው በቁጥጥር ስር ከዋሉ ግለሰቦች እስካሁን 92 ተሽከርካሪዎች እገዳ ተጥሎባቸዋል። ከእነዚህ ውስጥ ሁለቱ በአቶ ገብረዋህድ ባለቤት ኮረኔል ሃይማኖት ተስፋይ ስም የተመዘገቡ ሲሆኑ 54 የሚሆኑት ደግሞ በአቶ ነጋ ገብረእግዚአብሄር ስም የተያዙ ናቸው።
ከተሽከርካሪዎች አራቱ በኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉሙሩክ ባለስልጣን የአዳማ ቅርንጫፍ ስራ አሰኪያጅ በነበሩት አቶ አሞኘ ታገለ ስም የተመዘገቡ ሲሆን ከውጭ የሚመጡ ባለሃብቶች ወደ ሃገር ቤት እቃዎቻቸውን ሳያስፈትሹ እንዲያስገቡ በማድረግ በእነርሱና በጉሙሩክ የስራ ሃላፊዎች መካከል ጉቦ በማቀባበል መንግስትን ጎድቶ ራሳቸውን ጠቅመዋል በሚል በተጠረጠሩት በአቶ ዳዊት መኮንን ስም እንዲሁ አራት ተሽከርካሪዎች ተይዘዋል።
ሌሎች ሰባት ተሽከርካሪዎች በአልቲሜት ፕላን ሃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር ሲመዘገቡ ስድስት የሚሆኑት ተሽከርካሪዎች ደግሞ በኢትባ ኮንስትራክሽን ማሽነሪ አከራይ ሃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር ተመዝግበው ይገኛሉ።
የፌደራሉ የስነ ምግባርና የጸረ ሙስና ኮሚሽን የምርመራ ቡድን በተጠቀሱ ግለሰቦች፣ ድርጅቶችና ሌሎች አካላት እግድ የተጣለባቸው ተሽከርካሪዎች እንዳይሸጡ፣ እንዳይለወጡ እና ለሶስተኛ ወገን እንዳይተላለፉ አስደርጓል።
የእነ አቶ ገብረዋህድ ወልደጊዮርጊስና ሌሎች መዝገቦችን ሳያካትት በእነ መላኩ ፈንታ መዝገብ በተዘረዘሩ ተጠርጣሪዎች ተፈጸመ በተባለው የሙስና ወንጀል ከቀረጥና ታክስ ጋር በተያያዘ ከተገኙ ሰነዶች ብቻ መንግስት ከ230 ሚሊየን ብር በላይ ጉዳት እንደደረሰበት ነው የኮሚሽኑ መረጃ የሚያመለክተው።

No comments:

Post a Comment